የ COVID-19 ግብረ ሃይል በድንግል ማርያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ካቴድራል በሎስ አንጀለስ የቤተክርስቲያን ደጆች መዘጋትን ተንተርሶ ከቤተክርስቲያን አባላት ተውጣጥቶ ተቋቋመ። የግብረ ሃይሉ መረጃ በቤተክርስቲያናችን ካህናት ተነግሮ ነገር ግን ማንም ሰው ይሄ እርዳታ ያስፈልገናል ብሎ ስላልጠየቀ የቤተክርስቲያኒቱ የምግባረ ሰናይ ኮሚቴ አባላት ከግብረ ሃይሉ ጋር በመቀናጀት ቤተክርስቲያናችን አጠገብ በአዛውንት መኖሪያ ለሚኖሩ 12 ቤተሰቦች ጥቂት አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን በመላክ ጀምሮ አሁን አራተኛውን ዙር አጠናቋል። የሶስተኛውና የአራተኛው ዙር ላይ ማለትም ለሆሳዕና እና ለትንሣዔ ግን በከተማችን ውስጥ ለሚገኙ ከአርባ በላይ ለሚሆኑ ቤተሰቦች ተደራሽ ሆኗል። ዙር 5 ደግሞ በቅርቡ ይቀጥላል። ይህንን በጎ ተግባር ለመተግበር የበቃነው የሃይማኖተ አበው መዘምራን (ብዙዎቹ በግብረ ሃይሉ የተካተቱ)፥ የኢትዮጵያ ኮምዩኒቴ ማእከል በሎስ አንጀለስ፥ እና ጥቂት የቤተክርስቲያናችን አባላት በለገሱን ገንዘብ ነው።

ይህ ግብረ ሃይል ሦስት የተወራረሱ አካላት ጥምር ነው። ማለትም የድንግል ማርያም ምግባረ ሰናይ ወይም የበጎ አድራጎት ኮሚቴ፥ የድንግል ማርያም የሃይማኖተ አበው መዘምራንና የድንግል ማርያም COVID – 19 ግብረ ሃይል ናቸው። የዚህ እንቅስቃሴ አላማ፥ ከቁሳቁስ ማቀበል ሌላ የሃኪም ቀጠሮ ኖሯቸው መጟጟዣ ለሌላቸው ወይንም ከፋርማሲ መድሃኒት ማምጣት እርዳታ ለሚፈልጉ ሰዎችን መርዳት ነው።

እስከ ዛሬ ከተላኩት እቃዎች ውስጥ ለአብነት ያህል እንደ ውሃ፥ ስኳር፥ ጨው፥ ዘይት፥ ቡና፥ የመጸዳጃ ቤት ወረቀት፥ ወተት፥ የፕላስቲክ ጓንት፥ አፍና አፍንጫን የሚሸፍን ጭምብል፥ የመሳሰሉ ይገኙበታል። የትንሣዔ ዋዜማ ስጦታ ግን ለየት ያለ ነበር እሱውም ዶሮ ወጥ፥ እንጀራ፥ አይብ፥ የተነጠረ ቅቤ፥ የመሳሰሉ ነገሮች ይገኙበት ነብር። አንዳንድ ሰዎች ስጦታውን ሲቀበሉ ቤተክርስቲያን በዚህ ጭንቅ ጊዜ አስታወሰችን በማለት ምስጋናቸውን ከእንባና ከምርቃት ጋር ገልጸዋል።

ይሄ እንቅስቃሴ በቤተክርስቲያናችን አውደ ምህረትና በሕብር ሬዲዮ አንድ ሁለቴ ተገልጿል። ነገር ግን ቤተክርስቲያን የምታከናውነውን ተግባር አባላቷ በሰፊው እንዲገነዘቡት በድረ ገጻችን ላይ እንዲጫን አሰብን። በአካባቢያችን ያሉ የኢትዮጵያውያን ቁጥር በአርባና በሃምሳ የተወሰነ ስላልሆነ፥ የኛን የአንዲት ቤተክርስቲያን ጥቂት ልጆች የምናከናውነውን በጎ ተግባር እንደ ተሞክሮ ወስደው ተጨማሪ ሰዎች በየቀጠናውና በየከተማው ቢተባበሩ ብዙ ሰው ሊታደጉ እንደሚችሉ እምነታችን ነው። ይህንን እግዚአብሔር የሚወደውን ሥራ እንድንተገብር ስለፈቀደልን ክብር ምስጋና ለርሱ ይሁን።

በድንግል ማርያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ካቴድራል
የምግባረ ሰናይ ኮሚቴ

© 2016 Virgin Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Cathedral
Top
Follow us: